Sunday, July 14, 2013

የአንድ ኪሎ ቲማቲም ዋጋ 25 ብር ደረሰ

ምርት ላይቀርብ እንደሚችል ተጠቆመ
በአትክልትና ፍራፍሬ አምራችነታቸው በሚታወቁት የምሥራቅ ሸዋ ወረዳዎች ውስጥ በተከሰተው የቲማቲም እርሻ ውድመት ሳቢያ የቲማቲም ዋጋ ማሻቀቡን ቀጥሏል፡፡
ሰሞኑን በአዲስ አበባ የአንsድ ኪሎ ግራም ቲማቲም ዋጋ 25 ብር የደረሰ ሲሆን፣ ከዚህ በኋላም ዋጋው እየጨመረ ይሄዳል ተብሎ ተሰግቷል፡፡ በአሁኑ ወቅት በ25 ብር እየተሸጠ ያለውም ቢሆን ለቲማቲም እርሻ ውድመት ምክንያት በሆነው ቱታ አብሱሉታ በተባለው ትል የተወጋ ቲማቲም ነው፡፡
በመቂ አካባቢ ያሉ አርሶ አደሮች እንደሚገልጹት፣ ቱታ አብሱሉታ የሚባለው ትል ባይከሰት በአሁኑ ወቅት የአንድ ኪሎ ቲማቲም የችርቻሮ ዋጋ ከአምስት ብር አይበልጥም ነበር፡፡ ቱታ አብሱሉታ ከመስፋፋቱ በፊት በሚያዝያ 2005 ዓ.ም. አማካይ የአንድ ኪሎ ቲማቲም ዋጋ ስድስት ብር ነበር፡፡ ወዲያው ወደ 14 ብር ከዚያም ዋጋው እየጨመረ 25 ብር ደርሷል፡፡ ለአዲስ አበባ ገበያ ቲማቲም በማቅረብ ከሚታወቁት እንደመቂ ካሉ አካባቢዎች የሚገባው የቲማቲም ምርት ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ በአውዳሚው ትል የተወጋ ነው፡፡
ከአካባቢው የቲማቲም አምራቾች የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ ተመሳሳይ የነበረው አብዛኛው የቲማቲም ምርት የጠፋ ቢሆንም በተወሰኑ ማሳዎች ላይ ያለና በቱታ አብሱሉታ የተወጋው ቲማቲም በከፍተኛ ዋጋ እየተሰበሰበ ለገበያ እየቀረበ ነው፡፡ በሺዎች የሚቆጠሩ አርሶ አደሮችን ለኪሳራ የዳረገው የቱታ አብሱሉታ ትል ማጥፊያ መድኃኒት ባለመገኘቱ፣ በትሉ የተወጋውና አሁንም ለገበያ እየቀረበ ያለው ቲማቲም ተለቅሞ ካለቀ በኋላ አዲስ ምርት ስለማይኖር ዋጋው ከዚህም በላይ ይሆናል፡፡
መድኃኒት ያልተገኘለት የቱታ አብሱሉታ መስፋፋት ሊገታ ባለመቻሉ፣ አርሶ አደሮች በአጠቃላይ ቲማቲም ከመትከል ተቆጥበዋል፡፡
ከምሥራቅ ሸዋ ዞን አርሶ አደሮች ውጭ ከሌላ ቦታ የሚመረት ምርት ለገበያ የማይቀርብ ከሆነም ችግሩ የከፋ እንደሚሆን ጠቁመዋል፡፡ ይህ ከመሆኑ በፊት ግን ትሉን ሊያጠፋ የሚችል መፍትሔ በመንግሥት ደረጃ መታሰብ እንዳለበትም እኒሁ ያነጋገርናቸው አርሶ አደሮች ገልጸዋል፡፡
በሌላ በኩል ግን ትሉን ለማጥፋት ፍቱን መፍትሔ ነው ከተባለው ባዮሎጂካል መፍትሔ ሌላ ትሉን የሚያጠፋ መድኃኒት አለን የሚሉ ባለሙያዎች በአካባቢው የተለያዩ ሙከራዎችን እያደረጉ ነው፡፡

No comments:

Post a Comment